Ethiopian News and Views.

የመጅሊስ ምርጫ ውጤት እንዲታገድ ተጠየቀ

ጥቅምት 7 ቀን 2005 ዓ.ም.

እየተካሄደ ያለው የመጅሊስ ምርጫ ሕገ-ወጥ በሆነ አካል እየተከናወነ ስለሆነ የምርጫው ውጤት እንዲታገድ ተጠየቀ።  እገዳው የተጠየቀው የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎች በወከሏቸው ጠበቃ በቀረበ የፍትሐ ብሔር ክስ ነው።

በእስር ላይ የሚገኙት የኮሚቴው አባላት የወከሏቸው የሕግ ባለሙያ አቶ ተማም አባቡልጉ እንደገለጹት እየተካሄደ ያለውን ምርጫ ለማካሄድ ህጋዊ መሰረት የሌላቸው መጅሊሱ እና የኡላማዎች ምክር ቤት በመሆናቸው ውጤቱ እንዲታገድ ለከፍተኛው ፍርድ ቤት የልደታው ምድብ ሰባተኛ ፍትሐ ብሔር ችሎት ክስ መመስረቱን አስታውቀዋል።

ሁለቱ ተቋማት በ1996 ዓ.ም በወጣው የመጅሊሱ ህገ ደንብ መሠረት በየአምስት አመቱ ምርጫ እንዲካሄድ እና መጅሊሱ በህዝብ ተመርጠው እንደሚመሩ ቢገልጽም በደንቡ መሠረት ምርጫው እየተካሄደ ባለመሆኑ ውጤቱ እንዲታገድ በፍትሐ ብሔር ህግ አንቀጽ 408 እና በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 28 መሠረት ክስ መቅረቡን ገልጸዋል። የክሱ ዝርዝር እንደሚያመለክተው ምርጫው ከመስከረም 27 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጥቅምት 22 ቀን 2005 ዓ.ም የሚደረግ መሆኑን አስታውሶ ይህንን ለማሳገድ አቤቱታ በ22/01/2005 ዓ.ም ቀርቦ ነበር ብሏል። ነገር ግን ምርጫው መደረጉ መቀጠሉና ውጤቱ መገለጹ በከሳሾችና በወከላቸው ሕዝብ እንዲሁም በአጠቃላይ ህብረተሰቡ ላይ ሊተካ እና ሊካስ የማይችል ጉዳት ያስከትላል ብሏል።

በመሆኑም ይህ ክርክር የመጨረሻ እልባት እስኪያገኝ ድረስ በተከሳሾች በኩል እየተደረገ ያለው ምርጫ እንዲቆም (እንዳይካሄድ) እና የተደረገውን ውጤቱ እንዳይገለጽ (ውጤቱ ስራ ላይ እንዳይውል) ታግዶ እንዲቆይ እንዲታዘዝልን ሲሉ ጠይቀዋል።

Leave a Comment

© 2007-2012 Abbay Media ‘The Ethiopian Information Bank’

Scroll to top