Ethiopian News and Views.

በአንዋር መስጊድ ለጸሎት ከተሰባሰበው አማኝ ይልቅ ፖሊሶች እየበዙ ነው።

አባይ ሚድያ ዜና

መርካቶ የሚገኘው ታላቁ አንዋር መስጊድ በፖሊስ ኀይሎች ዙሪያውን መከበቡ በርትቷል። ምንም እንኳ የሙስሊሙ ኀብረተሰብ በመንግስት ላይ ያለውን ተቃውሞ በይፋ መግለጽ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ አንዋር በታጣቂዎች ጥብቅ ቁጥጥር ሲደረግበት ቢቆይም የዛሬው ግን ለየት ይል ነበር። የዛሬውን የጁምአ ስግደት በተለየ መልኩ በዛ ያሉ የፌዴራል ፖሊሶች አጥለቅልቀውታል። ከፍተኛ ቁጥር ያላው የእስልምና አማኝ እንደወትሮው በአንዋር ግቢ ውስጥ እና ውጭ ጸሎት የማድረግ ባህሉን ከተከለከለ ወራት አልፈዋል። በአሁኑ ወቅት የመስጊዱ አካባቢ የሽብር ቦታዎች ተብለው በመንግስት እጅግ ከሚጠረጠሩ ሥፍራዎች አንዱ ሆኗል። በዚህም ምክንያት ጸሎትና ስግደት በመስጊዱ ግቢ ውስጥ ብቻ እንዲከናወን መንግስት ግዴታ ጥሏል። ይሁንና ለተደጋጋሚ ሳምንታት አማኙ ሁሉ ቢጫ ጨርቅ ክንዱ ላይ በማሰር መንግስት በዓይማኖቱ የግል ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ መግባቱን በፍጥነት እንዲያቆም ቢያስጠነቅቁም ምላሽ አላገኙም። የማስጠንቀቂያው ቢጫ ጨርቅ ወደ ቀዩ የቁጣ ቀለም ይለወጣል ብሎ የሰጋው መንግስት ዛሬ መስጊዱን በከፍተኛ የታጣቂ ሀይል ሲያስጠብቅ እንደነበረ በግልጽ ታይቷል። ሰላማዊው ሙስሊም ኅብረተሰብ ግን በትዕግስት የተሞላውን ማስጠንቀቂያ በአንድነት ካሳየ በኋላ ጸሎቱን አጠናቆ ተበታትኗል። እነሱ ከተበታተኑ በኋላም ግን ፖሊሶች የመስጊዱን ዙሪያ ቶሎ ለቀው ከመሄድ ይልቅ አካባቢውን በዓይነቁራኛና በፍርሃት ሲፈትሹት ቆይተዋል።

Leave a Comment

© 2007-2012 Abbay Media ‘The Ethiopian Information Bank’

Scroll to top